Saturday, December 28, 2013

ትግሉ የሁሉንም ተሳትፎ የሚጠይቅበት ወሳኝ ምእራፍ ላይ ደርሷል


ራሱን የብሄረ አማራ ዲሞክራሲያዊ ንቅናቄ (ብአዴን) ብሎ የሚጠራው ድርጅት በከፍተኛ የፖለቲካ ኪሳራ ውስጥ ገብቷል። የህወሀትን ዙፋን ከመጠበቅ ባለፈ ምንም ሚና የሌላቸው የብአዴን  አመራሮች ያለፉትን ሶስት  ወራት በተለያዩ መንገዶች የድርጅቱን አባሎች ሲገመግሙ ከርመዋል። በግምገማዎች ላይ በግልጽ እንደታየው ብአዴን በክልሉ ከሚገኙ ወጣቶች አባሎቹ ጋር ሆድና ጀርባ ሆኗል፤ ወጣቶቹ በግልጽ “ዙፋን ጠባቂነቱ ይብቃ፣ ለውጥ እንፈልጋለን፣ ብአዴን ለ22 ዓመታት ተፈትኖ የወደቀ ድርጅት ነው” የሚሉ ጥያቄዎችን አንስተዋል። ለውጥ ፈላጊ ወጣቶች እየተጫወቱ ያለው ሚና በሌሎች የኢህአዴግ ድርጅቶች ውስጥ ላሉ ወጣት አባላት ጥሩ ትምህርት የሚሰጥ ነው።  ሰሞኑን በገሀድ በግምገማዎች ላይ ሲነገር እንደነበረው ብአዴን እወክለዋለሁ ከሚለው የአማራ ህዝብ ሙሉ በሙሉ ተነጥሎ በአየር ላይ የተነሳፈፈ ድርጅት እንዲሆን ወጣቶቹ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል።
ይህን እውነታ ዘግይተው የተረዱት የብአዴን ዙፋን ጠባቂ አመራሮች የሚይዙትን የሚጨብጡትን በማጣት የተለያዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ላይ ይገኛሉ። ታማኝ የሚሉዋቸውን ካድሬዎች በየወረዳዎች እና በየቀበሌዎች  በመላክ በግንቦት7 አባልነት ወይም ደጋፊነት የሚጠረጠሩትን ወይም የግንቦት7 አባሎች ናቸው ተብሎ ከሚገመቱ ሰዎች ጋር በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ግንኙነት አላቸው ተብሎ የሚጠረጠሩትን ሰዎች በመያዝና በማሰቃየት ሌላው ወጣት ተቃውሞውን እንዳይቀላቀል ለማድረግ እቅድ ነድፈው ለመንቀሳቀስ አስበዋል። እንዲሁም አንድ ለአምስት የተባለውን የመጠርነፊያ ስልት በመስሪያ ቤቶች፣ በቤተሰብ፣ በትምህርት ቤቶችና በተለያዩ ተቋማት ላይ በስፋት በማውረድ፣ የህዝቡን የእለት ተለት እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር አልመዋል።  የግንቦት7ን ህዝባዊ ሀይል ለመቀላቀል ቆርጦ የተነሳውን ወጣት እንቅስቃሴ ለመቆጣጠር የአካባቢ ፖሊሶችንና የድንበር ጠባቂዎች ሚሊሺያዎችን በማጠናከር እና በማብዛት ለመቆጣጠር ውሳኔ አሳልፈዋል። በድርጅቱ ውስጥ የግንቦት7 ደጋፊዎች ናቸው ተብሎ የሚጠረጠሩትን ወይም ለድርጅቱ ታማኝ አይደሉም የሚባሉትን ሁሉ በመመንጠር ብአዴንን እንደገና በእግሩ ለማቆም ውሳኔ አሳልፈዋል።
በጭካኔያቸው፣ በጎጠኝነታቸው፣ በንቅዘታቸው እና በሎሌነታቸው የሚታወቁትን ታማኝ ካድሬዎች ወደ ፊት በማምጣት ለድርጅቱ እስትንፋስ ለመስጠት ደፋ ቀና እያሉ ነው። ሰሞኑን የተደረገው ሹም ሽርም ከዚሁ ጋር የተያያዘ ነው። ጉልቻ ቢቀያየር ወጥ አያጣፍጥም እንደሚባለው የሰዎች መለዋወጥ የብአዴንን ህልውና ከመክሰም አያድነውም።
ለመሆኑ ብአዴን የህወሀትን ዙፋን ከመጠበቅ በስተቀር ባለፉት 22 አመታት እወክለዋለሁ ለሚለው ህዝብ ምን ሰራ? ሰፊው የአገራችን መሬት ለሱዳን ተላልፎ ሲሰጥ የስምምነት ፊርማውን ከማስቀመጥ፣ ህዝቡ ከቦታ ቦታ ሲፈናቀል፣ ለአመታት  በኤድስና በወባ  እንደቅጠል ሲረግፍ ፣ ወጣቱ ስራ አጥቶ በአደገኛ እጾች ደንዝዞና ተስፋ ቆርጦ የወጣትነት እድሜውን በከንቱ ሲያሳልፍ ብአዴን የት ነበር? አንድ የብአዴን ከፍተኛ አመራር በገሀድ እንዳመኑት  ድርጅቱ ከህዝቡ ጋር ሳይተዋወቅ 22 አመታት አልፈዋል።
ግንቦት7 መላውን የኢትዮጵያ ህዝብ ከዘረኛውና ዘራፊው የህወሀት ጎጠኛ አገዛዝ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ለመገላገል እና በምትኩ የሁሉም የምትሆን ዲሞክራሲያዊት ኢትዮጵያን ለመገንባት የጀመረውን ትግል ከመቼውም ጊዜ በላይ አጠናክሮ ቀጥሏል። በዚህ ወሳኝ የትግል ምእራፍ ወቅት የሁሉም ኢትዮጵያዊ ተሳትፎ እጅግ አስፈላጊ ነው። በተለይም በኢህአዴግ ድርጅቶች ውስጥ ታቅፈው በመንቀሳቀስ ላይ ያሉ እውነተኛ የስርአት ለውጥ እንዲመጣ የሚፈልጉ ሀይሎች የብአዴን ወጣት አባላት ከሚያደርጉት እንቅስቃሴ ልምድ በመቅሰም በውስጥ የሚያደርጉትን ትግል አጠንክረው እንዲገፉበት ንቅናቄያችን ጥሪውን ያቀርባል።
ድል ለኢትዮጵያ ህዝብ!!

No comments:

Post a Comment